በጁን ወር የኤልጂቢቲኪው+ ዜና ቅንብራችን፣ ፋጤ በጋና የተካሄደውን የፀረ-ኤልጂቢቲኪው ‘የቤተሰብ እሴቶች’ ጉባኤ፣ ኬፕ ቨርዴ ‘የተመሳሳይ ፆታ ወንድ አፍቃሪያን ገነት’ ናት የሚሉ አባባሎችን እና ከጋቦን፣ ደቡብ አፍሪካ እና ናይጄሪያ የተውጣጡ መነበብ ያለባቸው ታሪኮችንም ይዳስሳል።
በቤዛ ለዓለም
የኒጀር አዲሱ የወንጀል ሕግ ሥራ ላይ ከዋለ ጥቂት ሳምንታት ብቻ ቢሆነውም መዘዙ ከወዲሁ መታየት ጀምሯል። በአገሪቱ ታሪክ ለመጀመሪያ ጊዜ በተመሳሳይ ፆታ ግንኙነት ላይ ወንጀል በሚደነግጉ ድንጋጌዎች መሠረት ቢያንስ 16 ሰዎች ታስረዋል፤ ተሟጋቾችም በዋና ከተማዋ ኒያሜ ብዙ ኤልጂቢቲኪው ሰዎችን እንዲደበቁ ያደረገ እየተባባሰ የመጣ የፍርሃት ድባብ መፈጠሩን ይገልጻሉ።ለዓመታት ኒጀር ከበርካታ ጎረቤቶቿ ተለይታ ቆይታለች፤ በፈቃደኝነት የሚደረግ ተመሳሳይ ፆታ ግንኙነት ከዚህ ቀደም በግልጽ በሕግ አልተከለከለም ነበር።
ይህ ሁኔታ የተለወጠው ወታደራዊ መንግሥቱ በጁን ወር ሕጉን ሲያፀድቅ ነው። ሕጉ ለተመሳሳይ ፆታ ግንኙነት እስከ 10 ዓመት እስራት፣ ከኤልጂቢቲኪው ድርጅቶች እና ከተመሳሳይ ፆታ ጋብቻ ጋር በተያያዙ ተግባራት ደግሞ እስከ 20 ዓመት እስራት ደንግጓል። ከዚያ በኋላ እስራቶቹ በፍጥነት መጀመራቸው፣ ወንጀል አድርጎ መፈረጅ በምልክት ደረጃ ብቻ እንደማይቀር የሰብዓዊ መብት ድርጅቶች ለረጅም ጊዜ ሲሰጡት የነበረውን ማስጠንቀቂያ ያጠናክራል።አንድ አገር አዳዲስ የወንጀል ድንጋጌዎችን ከፈጠረች በኋላ፣ እነሱ የፖሊስ እርምጃ መሣሪያዎች ብቻ ሳይሆኑ የመገለል፣ የማስፈራራት እና የጠላትነት መሣሪያዎችም ይሆናሉ።
የማህበረሰብ ድርጅቶች እና የጤና ባለሙያዎች ክስ ይመሠረትብኛል የሚለው ፍርሃት በኒጀር ያሉ ሰዎችን የኤችአይቪ መከላከያ አገልግሎቶችን ከመፈለግ፣ ከእኩዮች ድጋፍ ከማግኘት ወይም ለረጅም ጊዜ ደህንነታቸው የተጠበቀ ቦታ ከሰጧቸው ቡድኖች ጋር ግንኙነት ከመቀጠል እያገዳቸው መሆኑን አስጠንቅቀዋል። ለአደጋ የተጋለጡ ግለሰቦች እርዳታ ለመፈለግ እየተቆጠቡ ሲሆን፣ ተሟጋቾችም ሥራቸውን በይፋ መቀጠል ወይም አለመቀጠል ላይ ከባድ ውሳኔ ለመወሰን ተገድደዋል።የኒጀር ልምድ በአንዳንድ የአፍሪካ ክፍሎች እየታየ ያለውን ሰፊ ለውጥ ያሳያል፤ አዳዲስ ሕጎች ተመሳሳይ ፆታ መቀራረብን ብቻ ሳይሆን የኤልጂቢቲኪው ማህበረሰቦች እንዲኖሩ የሚያስችሏቸውን መረቦች፣ ድርጅቶች እና አገልግሎቶችንም እያነጣጠሩ ነው።
በጁን ወር በክልሉ የፀረ-ኤልጂቢቲኪው ፖሊሲዎችን ለማራመድ የሚደረገው ግፊት ይበልጥ ተጠናከረ።በአራተኛው የአፍሪካ ፓርላማዎች መካከል የቤተሰብ እሴቶች እና ሉዓላዊነት ጉባኤ (African Inter-Parliamentary Conference on Family Values and Sovereignty — AICFVS) ላይ፣ ከ20 ገደማ አገራት የመጡ ተወካዮች በአክራ፣ ጋና ተሰብስበው፣ “የአፍሪካ የቤተሰብ እሴቶች” ተብለው በሚጠሩ መርሆዎች ላይ የተመሠረቱ ሕጎችን እንዲያጠናክሩ እና “የኤልጂቢቲ አጀንዳን” ያራምዳሉ ተብለው ከሚታዩ ዓለም አቀፍ ስምምነቶችና ውሎች — ከተባበሩት መንግሥታት ጋር ያሉትንም ጨምሮ — እንዲወጡ መንግሥታትን የሚጠይቅ ወደ ኋላ የሚመልስ ቻርተር እንዲደግፉ ተጠርተዋል።
ደቡብ አፍሪካ እና ሞዛምቢክ በመጨረሻው ውሳኔ ድምፀ ተአቅቦ ሲያደርጉ፣ 18 ልዑካን ቡድኖች ከዚህ ቀደም በዩጋንዳ በተካሄደ ጉባኤ የተዘጋጀው ቻርተር ወደ ፊት እንዲራመድ ደግፈዋል። ሰነዱ በሕግ አስገዳጅ ባይሆንም፣ በአህጉሪቱ ላይ በኤልጂቢቲኪው ሰዎች ላይ ሕግ ለማውጣት የሚደረገው የተቀናጀ ጥረት እየጨመረ መሆኑን ያሳያል፤ ቡርኪና ፋሶ እና ኢስዋቲኒም በ2027 የጉባኤውን ቀጣይ እትሞች እንዲያስተናግዱ ይጠበቃል።
ኢትዮጵያ በዘንድሮው ጉባኤ ተወካዮች እንደነበሯት ከሚታወቁ አገራት መካከል አልነበረችም። ሆኖም የኢትዮጵያ ፀረ-ኤልጂቢቲኪው ዘመቻ አድራጊዎች በቀደሙ ጉባኤዎች ውስጥ ጎልተው ታይተዋል።ከእነሱ መካከል ስዩም አንቶኒዮስ ይገኝበታል። እሱ በአሜሪካ ካሉ የጠንካራ ቀኝ ክንፍ ሃይማኖታዊ ቡድኖች ጋር ቅርብ ግንኙነት ያለው ሲሆን፣ የአክራሪው ክርስቲያናዊ ድርጅት ፋሚሊ ዎች ኢንተርናሽናል (Family Watch International) የአፍሪካ ዳይሬክተር ነው። ከዚህ ቀደም ተመሳሳይ ፆታ ፍቅርን “የሥነ-ምግባር ውድቀት ጫፍ” ብሎ ገልጾታል፣ ኢትዮጵያም “የተመሳሳይ ፆታ ፍቅር መቃብር” ትሆናለች ብሎ አውጇል።
ሆኖም ጁን ወር የኤልጂቢቲኪው መብቶች ወደ ኋላ የመመለስ አቅጣጫ በሁሉም ቦታ አንድ ዓይነት እንዳልሆነ እና ያለ ተቃውሞ እንዳልቀጠለ የሚያሳዩ ማስታወሻዎችንም አቅርቧል። በደቡብ አፍሪካ፣ አዲስ ጥናት የሕዝብ ተቀባይነት እያደገ መሆኑን አሳይቷል፤ አሁን 60 ፐርሰንት የሚሆኑት ተመሳሳይ ፆታ ወንድ እና ሴት አፍቃሪ ሰዎች ከሌሎች ዜጎች ጋር ተመሳሳይ መብቶች ሊኖራቸው ይገባል ይላሉ።በተመሳሳይ ጊዜ፣ የኬፕ ቨርዴን በንፅፅር እድገታዊ ሕጎች፣ ከፍተኛ የማህበራዊ ተቀባይነት እና እያደገ ያለ ታይነት ያጎሉ በርካታ ዘገባዎች፣ በአህጉሪቱ ካሉ በንፅፅር ተስፋ ሰጪ ቦታዎች አንዷ ላይ እንደገና ትኩረት አምጥተዋል። ነገር ግን አንዳንድ አርዕስተ ዜናዎች እንዳደረጉት ደሴቷን “የኤልጂቢቲኪው ገነት” ማለት ከእውነታው የራቀ ነው።
የፋጤ የወሩ ተሟጋች
በየወሩ ፋጤ በመላው አፍሪካ ለኤልጂቢቲኪው ማህበረሰቦች የሚቆሙ ሰዎችን ያከብራል። የዚህ ወር የክብር ተሸላሚያችን በኢስዋቲኒ የወሲባዊ እና የሥርዓተ-ፆታ አናሳዎች የበለጠ እውቅና እና ጥበቃ እንዲያገኙ ለዓመታት ባደረገችው ተሟጋችነት አስተዋፅዖ ያበረከተች አክቲቪስት ናት።
ሲሳንዳ ማቪምቤላ በወንዶች መካከል የሚደረግ ተመሳሳይ ፆታ ግንኙነት አሁንም በሕግ ወንጀል በሚባልበት፣ መድልዎ በሰፊው በሚታይበት እና ተሟጋቾች ከባድ እንቅፋቶች በሚገጥሟቸው አገር ውስጥ የኤልጂቢቲኪው ሰዎችን መብቶች እና ታይነት ለማራመድ በምታደርገው ቀጣይ ሥራ የፋጤ የወሩ ተሟጋች ናት።ማቪምቤላ የኢስዋቲኒ ሴክሹዋል ኤንድ ጀንደር ማይኖሪቲስ (Eswatini Sexual and Gender Minorities — ESGM) የፕሮግራሞች እና ተሟጋችነት ተባባሪ ዳይሬክተር ሲሆን፣ ቀደም ሲል የቡድኑ ዋና ዳይሬክተር ነበረች። ለዓመታትም የሰብዓዊ መብት ተሟጋች ሆና ሠርታለች።

የESGM ሕጋዊ እውቅና ለማግኘት ባደረገው ትግል ውስጥ በቅርብ ተሳትፋለች፤ ይህም ከሦስት ዓመት በፊት በአገሪቱ ከፍተኛው ፍርድ ቤት የተቀላቀለ ውጤት ያስገኘ ይግባኝን ያካትታል። መንግሥት የኤልጂቢቲኪው መብት ድርጅት እንዲመዘገብ መፍቀድ አለበት የሚለውን የፍርድ ቤቱን ውሳኔ ችላ ካለ በኋላም ማቪምቤላ በጽናት ቀጠለች።“ፍትሕ በቀላሉ አይገኝም፣” ብላለች፣ “አንዳንድ ጊዜም ፈጽሞ አይደረስበትም።” ሆኖም ተስፋ እንደማትቆርጥ ገልጻ፣ “የመደራጀት መብት… በሕገ መንግሥቱ መሠረት የሁሉም ስዋዚዎች መብት ነው” ብላለች።
የማቪምቤላ ትግል በመላው አፍሪካ ብዙ የኤልጂቢቲኪው ድርጅቶች የሚጋፈጧቸውን ችግሮች የሚወክል ሆኗል። ተሟጋቾች በሕጋዊ እርግጠኝነት እጦት እና በጭቆና መሃል ሥራቸውን በቀጠሉበት አገር፣ የእሷ ጽናት የማህበረሰብ መሪዎች አንድ መሠረታዊ ነገር — በይፋ የመደራጀት እና በሕዝባዊ ሕይወት ሙሉ በሙሉ የመሳተፍ ነፃነት — ለማግኘት ያላቸውን ቁርጠኝነት ያንፀባርቃል።
የጁን ወር አርዕስተ ዜናዎቻችንን በሙሉ ይዳስሱ
![]()
በኒጀር ሰፊው የፀረ-ኤልጂቢቲኪው የወንጀል ሕግ መሠረት እስራቶች ጀመሩ
![]()
የጋቦን ሕግ አውጪዎች በተመሳሳይ ፆታ ግንኙነት ላይ የወንጀል ቅጣቶችን መልሰው ለማስገባት እያጤኑ ነው
የጋና ጉባኤ አህጉር አቀፍ የፀረ-ኤልጂቢቲኪው ቻርተር ወደ ፊት እንዲራመድ አደረገ
የናይጄሪያ አፍሮቢትስ የሙዚቃ ዓለም ከኩዊርነት ጋር ካለው ያልተረጋጋ ግንኙነት ጋር እየታገለ ነው
ደቡብ አፍሪካ እና ሞዛምቢክ የፀረ-ኤልጂቢቲኪው ቻርተርን ከመደገፍ ድምፀ ተአቅቦ አደረጉ
ቡርኪና ፋሶ እና ኢስዋቲኒ የወደፊት የፀረ-ኤልጂቢቲኪው ጉባኤዎችን እንዲያስተናግዱ ተመረጡ
ኦክስፋም አፍሪካ ሠራተኞች የኤልጂቢቲኪው ቃላትን እንዳይጠቀሙ የሚያበረታታ መመሪያውን መልሶ ሰረዘ
በውጭ ገንዘብ የሚደገፉ ድርጅቶች ላይ ዩጋንዳ የጣለችውን ገደብ የኤልጂቢቲኪው ቡድኖች ተቃወሙ
በናይጄሪያ የኤችአይቪ ድጋፍ እየቀነሰ ባለበት ወቅት ፀረ-ተመሳሳይ ፆታ ወንድ አፍቃሪያን ‘ኪቶ’ ጥቃቶች ተባብሰዋል
የደቡብ አፍሪካ ጥናት የኤልጂቢቲኪው ሰዎች ተቀባይነት እያደገ መሆኑን አሳየ

